
አቶ አብዲ ጨምሮ 17 ተከሳሾች ” ከኛ ጋር ተከሰው የነበሩ እስረኞች ክስ ተቋርጦ እኛ ብቻ የምንታሰርበት ምንም ምክንያት የለም። በህገ መንግስቱ የተሰጠንን በእኩል የመታየት መብታችን የተነፈገ በመሆኑ ፍርድ ቤት አንቀርብም ” ሲሉ ተከሳሾቹ ማክሰኞ አቤቱታ ማሰማታቸው ይታወሳል።
በአቤቱታው ላይ ፍ/ቤቱ መርምሮ ትዛዝ ለመስጠት ለዛሬ በተያዘው ቀጠሮ ችሎቱ ተሰይሟል። ሆኖም ዛሬ አቶ አብዲ መሀመድን ጨምሮ በቃሊቲ ማረሚያ ቤት የሚገኙ 14 ተከሳሾች ችሎት አንቀርብም በማለት ሳይቀርቡ ቀርተዋል።
በዛሬው ችሎት ቂሊንጦ ማረሚያ ቤት የሚገኙ 3 ተከሳሾች በችሎት ቀርበው በአስገዳኝ ሁኔታ የቂሊንጦ ማረሚያ ቤት ወደ ፍ/ቤት እንዳመጣቸው አቤቱታአቅርበዋል። ከሌሎች ታራሚዎች ጋር ቃሊቲ እንዲዛወሩ እና አንድ ላይ ጉዳያቸው እንዲታይላቸው ጠይቀዋል። ፍርድ ቤቱ የደረሰባቸው የመብት ጥሰት ካለ በጽሁፍ እንዲያቀርቡ ብሏል።
የፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 2ኛ የፀረሽብርና ህገመንግስታዊ ጉዳዮች ወንጀል ችሎት አቶ አብዲ ኢሌን ጨምሮን አጠቃላይ ተከሳሾች ሌሎች እስረኞች ተፈተው እኛ ፍርድ ቤት የምንቀርብበት ምክንያት የለም ሲሉ ያቀረቡትን አቤቱታ በተመለከተ መርምሮ አቤቱታውን ማቅረብ ያለባቸው ክስ ላቋረጠው መንግስታዊ አካል እንጂ ለዚህ ችሎት አደለም፤ ጥያቄው የህግ መሰረት የሌለው ነው ሲል አቤቱታቸውን ውድቅ አድርጓል።በዚህም ፍርድ ቤቱ በያዘው ቀጠሮ የምስክር አሰማም ሂደት ይቀጥላል ሲል የዓቃቢ ህግ ቀሪ ምስክርን ለመስማት ለየካቲት 14 /2014 ዓ/ም ተለዋጭ ቀጠሮ ሰቷል። የቃሊቲ ማረሚያ ቤት ዛሬ ያልቀረቡ 14 ተከሳሾችን በቀጣይ ቀጠሮ እንዲያቀርብ አዟል።